እኔ በሃገሬ መፅሃፍት ሳስተምር ብዙዎቹ ጓደኞቸ ጠሉኝ፡፡ በዚህ ዘመን የባልንጀራ ፍቅር ጠፍቶ ነበርና ቅናት ያዛቸው፡፡
በትምህርትና ጓደኛን በመውደድ ከነርሱ እበልጣለው፡፡ ከሁሉ ሰው፤ ከፈረንጆቹና ከግብፃዊያን ጋር እስማማለሁ፡፡
መፅሃፍትን ሳስተምርና ስተረጉም እንዲህ እንዲህ ይላሉ፡፡ ግብፃዊያኖች ደግሞ (ኦርቶዶክሶች) እንዲህ እንዲህ ይላሉ
እላለው፡፡ እኛም ብንመረምር ይህን ሁሉ እናውቃለን እላለሁ እንጅ ይህ መልካም ነው ይህ ደግሞ ክፉ ነው አልልም፡፡
ግብፃቹ የፈረንጅ፣ ፈረንጆቹ ደግሞ የግብፃዊያኖቹ እመስላቸዋለው፡፡ ስለዚህ ሁሉም ጠሉኘ፡፡ ብዙ ጊዜም ወደንጉሱ
ከሰሱኝ፡፡ እግዚያብሔር ግን አዳነኝ፡፡ ከዚህም በኋላ ከአክሱም ካህናት አንድ ወልደ ዮሃንስ የተባለ ጠላቱ የንጉስ ወዳጅ
ስለነበረ፣ የነገስታት ፍቅር በሽንገላ ምላስ ስለሚያገኝ ወደ ንጉሱ ሄደ፡፡ ወደ ንጉሱም ገብቶ እንደዚህ አለው ፡፡
“ይህ ሰው ህዝብን ያሳስታል፡፡ ስለሃይማኖታችን እንነሳና ንጉሱን እንግደለው፣ ፈረንጆቹንም እናባራቸው ይላል”
እያለ ይሄንና ይሄን በመሰለ ውሸት ከሰሰኝ፡፡ እኔም ይህን አውቄ ገና ለገና ይገድለኛል ብዮ ፈርቼ የነበረኝን ሶስት ወቄት
ወርቅና የምፀልይበትን መዝሙረ ዳዊት ይዠ በሌሊት ሸሸሁ፡፡ ወዴት እነደምሄድ ለማንም አልተናገርኩም፡፡ ወደተከዜ በረሀ
ገባሁ፡፡ በነጋታውም ራበኝ፡፡ ከሀብታሞች ገበሬዎች እንጀራ ለመለምን እየፈራሁ ወጣሁ፡፡ ሰጡኝና በልቼ እየሮጥኩ ሄድኩ፡፡
እንዲህ እያልኩ ብዙ ቀን ቆየሁ፣ በኋላ ወደ ሽዋ ግድም ስሄድ ሰው የለለበት በርሃ አገኝሁ፡፡ ከገደሉ በታች መልካም ዋሻ
ነበርና ሰው ሳያየኝ በዚህ ዋሻ እኖራለሁ ብየ ወሰንኩ፡፡ ሱስንዮስ እስኪሞትም ድረስ በዚያ 2 ዓመት ቆየሁ፡፡ አንዳድንዴ
ወደገበያ እየወጣው ወይም ወደ አማሮች ሀገር እሄድ ነበር፡፡ ለአማራ ሰዎች የምበላው እንዲሰጡኝ የምለምን ባህታዊ
መነኩሴ እመስላቸው ነበር፡፡ ነገር ግን ሰዎች ከየት እንደምወጣና ወዴት እነደምገባ አያውቁም፡፡ ከዋሻየ ለብቻየ በሆንኩ
ጊዜም በመንግስተ ሰማያት የምኖር መሰለኝ፡፡ ቁጥር የሌለው ክፋታቸውን አውቄ ከሰዎች ጋር መኖር ጠላሁ፡፡ ሌሊት
መጥተው የበርሃ አራዊት እንዳይበሉኝም በድንጋይና በአሽዋ አጥር ዋሻየን አጠረኩ፡፡ እሚፈልጉኝ ሰዎች ወደኔ ቢመጡ
የማመልጥበት መውጫ አዘጋጀሁ፡፡ እዛ በሰላም ኖርኩ፡፡ በሚሰማኝ በእግዚያብሔር ተስፋ አድርጌ በሙሉ ልቤ በመዝሙረ
ዳዊት ፀለይኩ፡፡