እኔም እነደገና በሙሉ ልባችን በፍቅርና በዕምነት በትዕግስትም ወደ እርሱ በፀለይን ጊዜ እግዚያብሔርም ፀሎታችንን
እነደሚሰማ በሌላ መንገድ አወኩ፡፡ እኔ በልጅነት ጊዜየ ስለ እግዚያብሔር ሥራ ምንም ሳላስብ ወደ እርሱ ስፀልይ ሃጢያተኛ
ነበርኩ፡ ፡ለአዋቂ ፍጥረት የማይገባ ብዙ በደል በደልኩ፡፡ ስለሃጢያቴም ሰው ከእርሱ ሊያመልጥ ወደማይችለው ወጥመድም
ወደኩ፡፡ ፈፅሜ ልጠፋም ቀረብኩ፡፡ የሞት ፍርሃትም መጣብኝ፡፡ የዚያን ጊዜ ወደ እግዚያብሔር ተመልሼ እርሱ የማዳንን
መንገድ ያውቃልና እንዲድነኝ ብየ ወደ እርሱ መፀለይ ጀመረኩ፡፡ እግዚያብሔር ጌታ ሆይ ለሃጢያቴ እፀፀታለሁ ፈቃድህንም
ለማድረግ እፈልጋለሁ አልኩ፡፡በሙሉ ልቤም ብዙ ጊዜ ፀለይኩ እግዚያብሔር ሰማኝና ፈፅሞ አዳነኝ፡፡ ወደ እርሱ
ተመልሼም በፍፁም ልቤ አመሰገንኩት፡፡
በመዝሙረ ዳዊት "እግዚያብሔር የልመናየን ቃል ሰምቷል ወደድኩት" የሚለውንም ዘመርኩ፡፡ ደገምኩት፡፡ ይህም
መዝሙር ስለኔ የተፃፈ መሰለኝ፡፡ እንደገናም ልድን ካልሆነ በስተቀር አልሞትም፡፡ የእግዚያብሔርንም ሥራ እነግራለሁ
አልኩ፡፡ ነገር ግን ዘወትር ወደ ንጉስ የሚያሳጡኝ ነበሩ፡፡ ይህ ሰው ጠላትህ ነው ፤ ለፈረንጆቹም ጠላታቸው ነው ይሉታል፡፡
የንጉሱም ቁጣ በላየ እንደተቃጠለ አወኩ፡፡ አንድ ቀንም የንጉሱ መላክተኛ መጥቶ ንጉሱ ፈጥነህ ወደ እኔ ና ይልሃል አለኝ፡፡
እኔም እጅግ ፈራሁ፡፡ የንጉስ ሰዎች ስለሚጠብቁኝም ልሸሽ አልቻልኩም ባዘነ ልቤም ሌሊት በሙሉ ፀለይኩ፡፡ ሲነጋም
ተነስቼ ሄጄ ወደ ንጉሱ ገባሁ፡፡ እግዚያብሔርም የንጉሱን ልብ ስላራራው በፍቅር ተቀበለኝ፡፡ ስለፈራሁት ነገርም ምንም
አላለኝ፡፡ ነገር ግን ስለትምህርትና የመፅሃፍት ነገር ጠየቀኝ፡፡ አንተ የተማርክ ሰው ነህ፤ እነርሱም በጣም የተማሩ ናቸው፡፡
ፈረንጆቹን ትወዳቸው ዘንድ ይገባሀል አለኝ፡፡ ስለፈራሁትም እሺ ፈረንጆቹ በእውነት የተማሩ ናቸው አልኩት፡፡ ከዚህም
በኋላ ንጉሱ አምስት ወቄት ወርቅ ሰጥቶ በሰላም ሰደደኝ፡፡ ከንጉሱ ወጥቼ እተደነቅኩ ለኔ መልካም ስላደረገልኝ
13
እግዚያብሔርን አመሰገንኩት፡፡ እነደገናም ወልደ ዪሃንስ ባሳጣኝ ጊዜ ልሸሸው ስለተቻለኝ እንደፊተኛው እንዲያድነኝ
ሳልፀልይ ሸሸሁ፡፡ ሰው እግዚያብሔርን በከንቱ ሳይፈታተነው የሚቻለውን ሁሉ ሊያደርግ ይገባል፡፡ አሁን ግን ስለሸሸሁና
በዋሻየም ስለሁንኩ ቀድሞ ያላሰብኩትን እንዳስብና ለነፍሴም ትልቅ ደስታ እሚያስደስታት እውነትን እንዳወኩ፣ ወደ
ፈጣሪየ የመመለስ ፍፁምነት ምክንያት ስላገኝሁ ፈጣሪየን አመሰገንኩ፡፡ ፍርድህን እንዳውቅ ያሳመምከኝ ይገባኛል፡፡
ከመምህራን ጋር በነበረኩ ጊዜ ካስተዋለኩት ይልቅ ብቻየን በዋሻየ ሆኞ በጣም አስተውያለሁና፡፡ ይህም የፃፍኩት እጅግ
ትንሽ ነው፡፡ ይህን የመሳሰሉትን ብዙ እያሰብኩ በዋሻየ ቆየሁ፡፡ እግዚያብሔርም የፍጥረታቱን ምስጢር ለማወቅ ጥበብ
ስለሰጠኝ አመሰገንኩት፡፡ ነፍሴም የእግዚያብሔርን ጥበብ ሥራ ከማሰብ በቀር ሁሉን እየናቀች ወደ እርሱ ትሳብ ነበር፡፡
በሰፊው ልቤም በዳዊት መዝሙር ሁልጊዜ እፀልይ ነበር፡፡ ይህ ፀሎት በጣም ይጠቅመኛልና ሕሊናየንም ወደ እግዚያብሔር
ያነሳሳልኛል፡፡ በመዝሙረ ዳዊት ከሕሊናየ ጋር የማይስማማ ባገኝሁ ጊዜ እኔ ተርጉሜ በዕውቀቴ አስማማዋለሁ፡፡ ሁሉም
ያምርልኝ ነበር፡፡ እንደዚህ እያልኩ በፀለይኩም ጊዜ በእግዚያብሔር መታመኔ ይጨምር ነበር፡፡ ሁልጊዜም እንደዚህ እል
ነበር፡፡
"ጌታ ሆይ ፀሎቴን ስማኝ፡፡ ልመናየንም ችላ አትበል፡፡ ከሰው ልጆች ግፊትም አድነኝ፡፡ ጌታ ሆይ ይቅርታህን ከኔ አታርቅ፡፡
ምህረትህም፣ ፅድቅህም ዘወትር ያግኙኝ፡፡ ጌታ ሆይ ምኞቴን ሁልጊዜ እንድትሰጠኝም አልፈር፡፡ እንዲሁም እያልኩ ስምህን
ለዘላላም እዘምራለሁ፡፡ ወደ እኔ ተመልከትና ይቅር በለኝ፡፡ ለባሪያህ ሃይል ስጠው፡፡ የደህንነት ምልክት ከኔ ጋር አድርግና
የባሪያህንም ልጅ አድነው፡፡ ስለስምህም ምራኝና መግበኝ፡፡ ነፍሴን ከሃጢያን ጋር አትሳባት፡፡ ምህረትህም ከበላየ ትሁን፡፡
ባንተ ላይ ታምኛለሁና በንጋት እሚሰማ ምህረትን አድርግልኝ፡፡ በምድር ላይ ብፁዕ አድርገህ ጠብቀኝ፡፡ በጠላቶቼም እጅ
አታግባኝ፡፡ ከተስፋየ አታሳፍረኝ፡፡ ተድላና ደስታ አሰማኝ፡፡ እነርሱ ይገረማሉ አንተ ግን ባርክ፡፡ ይህም በጅህ እንደሆነ
አወኩ፡፡"
ይህንንና የሚመስለውን በሙሉ በልቤ ቀንና ሌሊት እፀልይ ነበር፡፡ ስለፀሎት ስጋዊና መንፈሳዊ ሥራ ጠዋትና ማታ
የምፀልየው ፀሎትም እንዲህ ነበር፡፡
"ፈጣሪየና ጠባቂየ ሆይ እሰግድልሀለሁ በሙሉ ልቤም እወድሀለሁ በዚች ለሊትም ላደረክልኝ መልካምም አመሰግንሀለሁ፡፡
ሲነጋም በዚች ቀን ጠብቀኝ እልሀለሁ፡፡ ሲመሽም በዚችኛዋ ለሊት በዚችኛዋ ቀንና በሕይወቴ ዘመን ሁሉ ፈቃድህን በእኔ ላይ
እንዳውቀውና እንድፈፅመው አዋቂ አድርገኝ፡፡ ሃጢያቴንም ይቅር በለኝ፡፡ ለሕይወቴ የሚያስፈልገኝንም የሚበቃኝን ሁልጊዜ
14
ስጠኝ፡፡ አንተን በመታመን ዘወትር አፅናኝ ጌታየ ሆይ ስለቸርነትህና ስለሃይልህ ስለታላቅነትህም ከሰው ምላስና እጅ፣
ከድህነትና ከደዌ ስጋ፣ ከነፍስ ሃዘንም አድነኝ፡፡ ደግሞም ባንተ ታመንኩ" የሚለውን በመዝሙር ያለውን እፀልይ ነበር፡፡
እንደገናም ፀሎት ብቻውን አይጠቅመኝምና ለህይወቴ የሚያስፈልገኝን በተቻለኝ ሁሉ ልሰራና ልደክም ይገባኛል ብየ
አሰብኩ፡፡ ነገር ግን ስራ አላውቅምና በእግዚያብሔር ሃይል እገባለሁ፡፡
"ጌታ ሆይ ስራየም አለበረከትህ ምንም አይጠቅመኝም፡፡ ሃሳቤን፣ ኑሮየን፣ ሥራየን አንተ ባርከው፡፡ አንተ በምታውቀው
መንገድ ደስታንና ገንዘብን ስጠኝ፡፡ከኔ ጋር በሥራ ያሉ ሰዎችን ልብ ወደ መልካም መልስልኝ፡፡ ሁሉ በተባረከው ፈቃድህ
ይሆናልና ለኔም የሽምግልናየን ጊዜ አሳምርልኝ፡፡"
ልባችን ዘወትር በእግዚያብሔር እጅ እንደሆነ አወቅኩ፡፡ በበሽታና በድህነት በችግርም መካከል ብንኖር እግዚያብሔር ብፁአንና
ደስተኞች ሊያደርገን ይችላል፡፡ እነደገናም በዚህ አለም በሃብትና በደስታ ሁሉ መካከል ብንኖር ጎስቋሎች ሊያደርገን ይችላል፡፡
ስለዚህም ድሆችና ችግረኞች በልባቸው ደስታ ሁልጊዜ ሲጫወቱ እናያለን፡፡ ሀብታሞችና ነገስታትም በምኞታቸው ብዛት
በሀብታቸው መካከል ሲያዝኑና ሲጎሳቆሉ እናያለን፡፡ እኛ ሳናውቀውና ሳንፈልገው የመነሻ ምክንያቱን ሳናውቅ ሀዘን በልባችን
ውስጥ ይመጣል፡፡ በምድር ብፁኣን እንዲያድርገንና ፍስሃና ደስታ እንዲሰማን ወደ እግዚያብሔር ልንፀልይ ይገባናል፡፡
እግዚያብሔር ለፃድቃን ብርሃን፣ ልባቸው ለቀና ደስታን ይሰጣቸዋል፡፡ እርሱ ያውቃልና የልባችንንም መንገድ ሁሉ ይገዛል፡፡
እርሱ በችግራችን ደስተኞች በድሎታችንም ሀዘንተኞች ሊያደርገን ይችላል፡፡ እግዚያብሔር እሚሰማን እንጂ ለሰዎች
እንደሚመስላቸው በደስታና ሀዘን አይደርሰንም፡፡ አንተ ፈጣሪየና ጌታየ በምድር እስካለህ ድረስ ብፁዕ አድርገኝ ደስታና
ትፍስህትንም አሰማኝ፡፡ ከሞቴ በኋላም ወደ አንተ ወስደህ ከአንተ አስጠጋኝ አልኩ ፡፡ እንዲህ ብየ ቀንና ለሊት እየፀልይኩ
እግዚያብሔርን ስነ ፍጥረትን፣ እንስሳትን፣ የበርሃ አራዊትን በየስርዓታቸው እያደነቅሁ ነበር፡፡ እነሱ ግን ሕይወታቸውን
ለመጠበቅና ዘራቸውን ለማራባት በፀባየ ተፈጥሯቸው ይሳባሉ፡፡ እንደገናም የበረሃ እንጨትና ሣር በትልቅ ጥበብ የተፈጠሩ
ይበቅላሉ፣ ይለመልማሉ፣ ያብባሉ በየወገኖቻቸውም የዘራቸውን ፍሬ አለ ስህተት ያወጣሉና ነፍስ ያላቸው ይመስላሉ፡፡
እንደገናም ተራሮችና ኮረብቶች ፣ ወንዞችና የውሃ ምንጮች ሥራ ሁሉ ስምህን ያመሰግነዋል፡፡ጌታየ ሆይ ስምህን በሁሉ
በሰማይ እና በምድር እጅግ ተመስግኗል፡፡ ይህ የእጅህ ስራ ፀሀይ የብርሀንና የዓለም ህይወት ምንጭ እጅግ ትልቅ ነው፡፡
አንተ የሰራሃቸውን፣ የመሰረትካቸውን ጨረቃና ከዋክብትን አንተ ከሰራህላቸው መንገድ ሌላ አለመዛነፋቸው በጣም
ያስደንቃሉ፡፡ በመራቃቸው ደቃቃዎች የሚመስሉ ከዋክብትን ቁጥራቸውን፣ እርቀታቸውን፣ ታላቅነታቸውንስ የሚያውቅ
ማነው? ደመናዎችም ልምላሜን ለማብቀል ውሃዎች ያፈሳሉ፡፡ ይህ ሁሉ ታላቅና እጅግ የሚያስደንቅ ጥበብ በጥበብ
የተፈጠረ ነው፡፡ እንደዛም ብየ ፈጣሪየን እያደነኩና ፈጣሪየን እያመሰገንኩ ሁለት ዓመት ተቀመጥኩ፡፡
15
እንደገናም የእግዚያብሔር ስራ እጅግ መልካም ነው፡፡ ሀሳቡም ትልቅና የማይነበብ ነው ብየ አሰብኩ፡፡ እንግዲያስ ትንሹና
ምስኪኑ ሰው ለሰው ጥበቡንና እውነቱን እንደገለፀለት ከእግዚያብሔር ዘንድ ተልኬ መጣሁ እያለ ስለምን ይዋሻል? ፈጣሪ
ታላቅነቱን እንድናውቅ ከሰጠን ህሊና ይልቅ እጅግ ዝቅ ያለና የተናቀ ግዑዝ ባህሉን ካልሆነ በቀር ሊገልፅልን አይችልም፡፡
ጌታ ሆይ እኔ በፊትህ ደህና ምስኪን ነኝ፡፡ ስላንተ የማይገናኝን እንዳውቅና ታላቅነትህን እንዳደንቅ አዲስ ምስጋና ሁልጊዜ
እንዳመሰግንህ ልቦና ስጠኝ፡፡